Tuesday, September 2, 2014

በአገሪቱ መግቢያና መውጫ ኬላዎች የኢቦላ ቅኝት ተጀመረ

በአገሪቱ መግቢያና መውጫ ኬላዎች የኢቦላ ቅኝት ተጀመረ 

በሞያሌ፣ በመተማ፣ በሁመራ፣ በቶጐ ጫሌና በጋምቤላ ከኢቦላ ጋር በተያያዘ ቅኝት መጀመሩን፣ የብሔራዊ ኮሚቴው አባልና የኢትዮጵያ የምግብ የመድኃኒትና የምግብ ክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር ባለሥልጣን የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት አስታወቀ፡፡ 
የቅኝት ሥራው ከጥቂት ቀናት በፊት የተጀመረው ለሚመለከታቸው የክልልና የፌደራል የጤና ባለሙያዎች አስፈላጊው ሥልጠና ከተሰጠ በኋላ መሆኑን ለሪፖርተር የገለጹት የጽሕፈት ቤቱ ኃላፊ አቶ አበባው ገሠሠ ናቸው፡፡ በአጠቃላይ የአገሪቱ መግቢያ መውጫ ኬላዎች ላይ ቁጥጥር ማድረግ አስፈላጊ ቢሆንም፣ የተጠቀሱት ኬላዎች ላይ ልዩ ትኩረት በማድረግ ቅኝቱ መጀመሩን አስረድተዋል፡፡ አሁን በተወሰነ ደረጃ የተጀመረው ቅኝት መጠናከር እንደሚገባውም ጠቁመዋል፡፡
በጋምቤላ ክልል ከስደተኞች ጋር በተያያዘ ትኩረት መስጠት ቢያስፈልግም፣ በጋምቤላ ኬላ ባለመኖሩ በባለሥልጣን መሥሪያ ቤቱ ጅማ ቅርንጫፍ ሥር ያሉ ኬላዎችን ለቅኝት ሥራው ለመጠቀም ሥራዎች መጀመራቸውን አመልክተዋል፡፡
አቶ አበባው እንዳሉት፣ የቅኝት ሥራው በሚሠራባቸው ኬላዎች ላይ የኅብረተሰብ ጤና ኮሚቴዎች  ተቋቁመዋል፡፡ ኬላዎቹ ላይ የቅኝት ሥራ መጀመሩ በሞያሌ፣ በመተማ ወይም በሁመራ በኩል ወደ ኢትዮጵያ ድንበር አቋርጠው በሚገቡ ሰዎች ላይ ትኩረት በማድረግ የቫይረሱን ሥርጭት ለመከታተል ብቻም ሳይሆን፣ በቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ወደ አገር ውስጥ ገብተው ወደተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች የሚሄዱ፣ በተለይም ለኢቦላ ተጋላጭ ከሆኑ አገሮች የሚመጡትን የቫይረሱ ምልክት ለ21 ቀናት ስለማይታይ ለመከታተል ያስችላል፡፡ ይህ ደግሞ የመከላከል ሥራውን ያጠናክረዋል ብለዋል፡፡ 
ከቫይረሱ ጋር በተያያዘ ያለው አካባቢያዊ እውነታ ታሳቢ እየተደረገ ዕርምጃዎች እንደሁኔታው ተለዋዋጭ እንደሚሆኑ የጠቆሙ ሲሆን፣ በኬንያ ሞያሌና በሌሎች ኬላዎች ላይ ከቅኝት አልፎ ምርመራ (ስክሪኒንግ) ማድረግ ቢያስፈልግ፣ ይህን የሚያስችል ዝግጅትና አቅም ስለመኖሩ ለአቶ አበባው ጥያቄ ቀርቦላቸው ለሪፖርተር በሰጡት ምላሽ፣  -የመከላከያ መሣሪያዎች ተዘጋጅተዋል፡፡ ሌሎችም የተሠሩ ሥራዎች አሉ በመገዛት ላይ ያሉ ነገሮችም አሉ፤›› ሲሉ አስረድተዋል፡፡
የዓለም የጤና ድርጅት ኬንያ በከፍተኛ ደረጃ ለኢቦላ ተጋላጭ መሆኗን በማስታወቁ ምክንያት፣ በምሥራቅ አፍሪካ የቫይረሱን ሥርጭት ለመከላከል ቁጥጥሮችና የመከላከል ዕርምጃዎች እየተወሰዱ ነው፡፡ አገሪቱ በዚህ ደረጃ ለቫይረሱ ተጋላጭ ናት የተባለችው ከምዕራብ አፍሪካ ወደ ምሥራቅ፣ ከምሥራቅም ወደ ምዕራብ አፍሪካ የሚደረግ ጉዞ መተላለፊያ በመሆኗ ነው፡፡
የዓለም የጤና ድርጅት ነሐሴ 22 ቀን 2006 ዓ.ም. በምዕራብ አፍሪካ ለተከሰተው የኢቦላ በሽታ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ እያደረገ ያለውን ምላሽ ለመምራትና ለማቀናጀት የሚያስችል ፍኖተ ካርታ ማዘጋጀቱን ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡ የፍኖተ ካርታው ዓላማ ከስድስት እስከ ዘጠኝ ወራት በሚሆን ጊዜ ውስጥ የቫይረሱን ቀጣይ ዓለም አቀፍ ሥርጭት መግታት ነው፡፡
ፍኖተ ካርታው በቫይረሱ የተጠቁ አገሮች የጤና ባለሙያዎችን ጨምሮ የአፍሪካ ኅብረትን፣ የልማት ባንኮችን፣ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ኤጀንሲዎችን፣ የሜዲስን ሳንፍሮንቲየርስና የገንዘብ ድጋፍ የሚያደርጉ አገሮችን አስተያየት ከግንዛቤ ያስገባ ነው፡፡
በኢትዮጵያ የኢቦላ ምልክት ለሚታይባቸው መታከሚያ የተለየ ሆስፒታል መዘጋጀቱን፣ የኢቦላ ቫይረስን ለመከላከል የሚደረገውን እንቅስቃሴ ይመራ ዘንድ ብሔራዊ ኮሚቴ ፡
መቋቋሙ ይታወሳል ፡፡

 

No comments:

Post a Comment